Tuesday, September 7, 2021

ሎጊታና ገላና የሲዳማ ጸጋዎች፤ የኢትዮጵያ አዲስ ሀብቶች

 ሎጊታና ገላና የሲዳማ ጸጋዎች፤ የኢትዮጵያ አዲስ ሀብቶች 


(ተጓዡ ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም ሲዳማ ክልል ስደርስ ድባቡ ሁሉ የእናት ሀገር ጉዳይ ነው፡፡ የሲዳማ ልቡ ሰሜን ኢትዮጵያ ዘልቋል፡፡ መንደሮቹ ለሀገር መከላከያ ሠራዊት ደጀን ለመሆን ያላቸውን ይለግሳሉ፤ ከተሞቹ ወኔ ቀስቃሽ ናቸው ሲል እስከ ሎጊታና ገላና ፏፏቴዎች ያደረገውን ጉዞ እንዲህ ያጋራናል፡፡)



(ሄኖክ ስዩም -ድሬ ቲዩብ)

ሲዳማ ነኝ፡፡ የገባሁበት ሁሉ በሀገር ጉዳይ መንፈስ ታውዷል፡፡ የሲዳማ ልቡ ሰሜን ላይ ነው፡፡ የእናት ሀገሩን ውሎ ያደምጣል፡፡ ብዙ ቦታዎች ስለ ሀገር ፍቅር፣ ስለጁንታው መደምሰስ የሚገልጹ ጽሑፎችን አይቻለሁ፡፡

ከሀዋሳ ደቡብ ምስራቅ አቅጣጫ 119 ኪሎ ሜትር ተጉዤ የደርስኩበት ይህ ስፍራ የሲዳማ ሌላ ውበት በድንቅ የፏፏቴ ዜማ የሚደመጥበት ቀዬ ነው፡፡ አዲሱ ክልል በነባሩ የሀገራችን የቱሪዝም ልማት ላይ ብዙ ድብቅ ገጸ በረከቶችን ይዞ የመጣ ነው፡፡ አንዱ ጋር ደርሻለሁ፡፡

ቦና ወረዳ ይባላል፡፡ እዚህ አስደናቂዎቹ መስህቦች ይታያሉ፡፡ አሁን እኔ ሎጊታ ስር ቆሜያለሁ፡፡ ሎጊታ ከአርቤጎና ምድር ከጋራምባ ተራራ የሚመጣ ወንዝ ነው፡፡ እንዲህ ያለ ቦታ ሆኖ የሚታየውን ተአምርና አስደናቂ ሁኔታ የትም የለም፡፡

አካባቢው ውብ ነው፡፡ የሎጊታ ወንዝ ድንቅ መልከዓ ምድር ፈጥሯል፡፡ አካባቢው ውብና ለመንገድ ቅርብ ነው፡፡ ያቆሙትን መኪና በርቀት እያዩ የሚጎበኙት ፏፏቴ መሆኑ ከሀገሬ ፏፏቴ ልዩ ያደርገዋል፡፡

የሎጊታን ወንዝ ጉዞ ተከትዬ ሌላ ስፍራ ደረስኩ፡፡ ጋላና ወንዝ ደግሞ ሌላ ፏፏቴ ሰርቷል፡፡ አንድ ጊቢ ሁለት የታላላቅ ወንዝ ፏፏቴዎች አንዱ ጋር ሲደርሱ የሌላው ድምጽ እየሸኘ ውበት የሚታይበት፡፡

እነኚህ ሁለት ወንዞች ከፏፏቴዎቻቸው ግርጌ አንድ ሆነው ይዋህዳሉ፡፡ የሚዋህዱበት አፋፍ ቆሜ አየሁ፡፡ ጋላና እና ሎጊታ ስማቸው ከዚህ በኋላ አንድ ነው፡፡ ገናሌን ፈጥረዋል፡፡ ገናሌ ከጋራምባ መሀጸን ብዙ ምንጭ ሆኖ በተበተነ ውበት ሁለት ወንዝና ፏፏቴ ሆኖ በአንድ ስም ለመጠራት አንድ ወንዝ የሚሆንበት ስፍራ፤

ገናሌ ተጓዥ ወንዝ ነው፡፡ መንገደኛነቱን ከሚያሳዩን መረጃዎች አንዱ 858 ኪሎ ሜትሮችን የሚፈስ መሆኑ ነው፡፡ ከዚያ ውስጥ በእናት ሀገር ምድሩ 480 ኪሎ ሜትሮችን ይጓዛል፡፡ እነሆ እዚህ አንድ ብሎ እና ገናሌ ተብሎ ከሎጊታና ከገላና ወንዞች ተዳቅሎ ሲፈጠር እያየሁ ነው፡፡

የቀድሞዎቹ የባሌና ሲዳሞ ጠቅላይ ግዛቶች ድንበር የዛሬው የገናሌ ዳዋ ሃይል ማመንጫ ሀብት የሚፈጠርበት ቆሞ እንዲህ ማሰብ ደስ ያሰኛል፡፡

ወልመልና ወይብን ተቀላቅሎ ወደ ጁባ የሚገባው ወንዝ ምንኛ ደጋ ምድር ፈጠረው ብዬ ሌላ ስፍራ ለማየት ጓጓሁ፡፡ እናም ወደ ሲዳማ ደጋ ምድር ለመውጣትና የአርቤጎናን ምንጮች ለመመልከት ልጓዝ ነው፡፡

ግቢውን ለቅቄ ስወጣ ይከተለኝ የነበረው የጋላና ፏፏቴ ድምጽ ለሎጊታ ፏፏቴ አቀብሎኝ እስከ አስፋልቱ ጎዳና ሸኘኝ፡፡

አሁን አብረን ደጋማው የሲዳማ ምድር እንጓዛለን፡፡ በረደኝ የለም በሻፌታ ይቀርባል፡፡ የእርጎ ሀገር ነው፡፡ ንጹህ ቅቤ የሚገኝበት፡፡ የሲዳማ ጎጆ ለእንግዳ ቸር ነው፡፡ ያንን ለማየት እነዚህ መንደሮች መግባት ይጠይቃል፡፡


https://news.et/2021/09/03/%e1%88%8e%e1%8c%8a%e1%89%b3%e1%8a%93-%e1%8c%88%e1%88%8b%e1%8a%93-%e1%8b%a8%e1%88%b2%e1%8b%b3%e1%88%9b-%e1%8c%b8%e1%8c%8b%e1%8b%8e%e1%89%bd%e1%8d%a4-%e1%8b%a8%e1%8a%a2%e1%89%b5%e1%8b%ae%e1%8c%b5/

No comments:

Post a Comment